ሚ/ር ጊልበርት ችዙካ እና ሚስ ደርካስ ኢሉንጋ ችልሸ የባለስልጣኑን የመገናኛ ብዙኃን ክትትልና ድጋፍ የሥራ ሂደት እንቅስቃሴን ተዘዋውረው የተመለከቱ ሲሆን ልዩ ልዩ ጥያቄዎችም አንስተው ምላሽና ማብራሪያ በባለሙያዎች ተሰጥቷቸዋል፡፡
የባለስልጣኑ የብሮድካስት አገልግሎት የክትትልና ድጋፍ ባለሙያዎች በበኩላቸው ባለስልጣኑ ባለው ልዩ መሳሪያ /ሰርቨር/ በመታገዝ እስከ ስድስት ወራት ድረስ የቅጅ ፕሮግራሞችን በናሙና በመምረጥና በኮምፒውተሮቻቸው ላይ መልሰው በመጫን ጥሰት መፈፀም ወይም አለመፈፀሙን ያረጋግጣሉ፡፡
በምን ያህል ቋንቋዎች የሚተላለፉ ፕሮግራሞችን ነው ለመሆኑ የምትከታተሉት ተብለው በልኡካን ቡድኑ ተጠይቀው ኢንስፔክተሮች ሲመልሱ ሀገራችን ውስጥ ካሉ 80 የብሔርብሔረሰብ ቋንቋዎች 40 ያህሉ ሕብተሰቡን ለማሳወቅ፣ ለማስተማርና ለማዝናናት በኤፍ ኤም ጣቢያዎች በሥራ ላይ እንደዋሉ ገልፀዋል፡፡
በብሮድካስት አገልግሎት በሚተላለፉ ፕሮግራሞች ላይ ጥቆማ ተቀብሎ በማጣራት በኩል ምን ያህል ሰርታችኋል ተብሎ ለተጠየቀው ጥያቄ ባለስልጣኑ ከተለያዩ ግለሰቦች፣ ድርጅቶች፣ ማኀበራት፣ ወዘተ የሚቀርቡለትን ቅሬታዎችና ጥቆማዎች ተቀብሎ ምላሽ በመስጠት ላይ እንደሚገኝ ባለሙያዎቹ ገልፀዋል፡፡
ባየነው የሞኒተሪንግ መሳሪያ እና በኢንስፔክተሮች ጥንካሬና ትጋት በእጅጉ ተደምመናል ያሉት ኢሉንጋ አያይዘውም ሀገራቸው ዛምቢያ ከኢትዮጵያ የብሮድካስት አሠራር ብዙ የምትማረው ነገር እንዳለ ጠቁመዋል፡፡ "ተልዕኮአችን የባለስልጣኑን የክትትልና ድጋፍ ሥራዎች ተዘዋውሮ መመልከትና ትምህርት መቅሰም ነበር፡፡ ያን ዛሬ በሚገባ አይተናል" ያሉት ደግሞ ሚ/ር ችዙካ ነበሩ፡፡ በሚዲያ ክትትልና ድጋፍ ሥራ ውስጥ ተግዳሮቶች ይኖራሉ ሆኖም ዋናው ነገር እነሱን በጥበብና በብልሀት ማለፍ ነው ብለዋል፡፡
ባለስልጣን መ/ቤቱ እና የዛምቢያ ማስታወቂያ ሚኒስቴር በመገናኛ ብዙኃን ዙሪያ ልምድ ሲለዋወጡና በቅርበት ተጋግዘው ሲሰሩ መቆየታቸው ታውቋል፡፡ |