የኢትዮጵያ ብሮድካስት ባለሥልጣን አጠቃላይ ሁኔታ
የኢትዮጵያ ብሮድካስት ባለሥልጣን በተሻሻለው የብሮድካስት አዋጅ ቁጥር 533/99 የተቋቋመ የፌዴራል መንግሥት መ/ቤት ነው፡፡ በተጨማሪ የመንግሥት ኮሙኒኬሽንን ጉዳዮች ጽ/ቤትን ለማቋቋም በወጣው አዋጅ 158/2001 አንቀጽ 11 መሠረት የሕትመት ሬጉላቶሪ ስልጣን ተሰጥቶታል፡፡ በዚህም ከአንድ ክልል በላይ ለሚሰራጩ የሕትመት ሥራዎች የምዝገባ የምስክር ወረቀት ይሰጣል፡፡ ተጠሪነቱም ለጠቅላይ ሚኒስር ሲሆን ቦርድ፣ ዋና ዳይሬክተር፣ ም/ዋና ዳይሬክተር፣5 ዳይሬክቶሬቶች፣6 ማስተባበሪያዎች እና አስፈላጊ ሠራተኞች አሉት፡፡
የባለሥልጣን መ/ቤቱ ዋና ዓላማ ለፖለቲካዊ፣ ለማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ዕድገት አስተዋጽእ የሚያደርግ ጥራቱ የተጠበቀ ቀልጣፋና አስተማማኝ የብሮድካስት አገልግሎት እንዲስፋፋ ማድረግና መቆጣጠር ነው::
የባለሥልጣኑ ዋና ዋና ተግባርና ኃላፊነቶች የመገናኛ ብዙሃን ለማኅበራዊ፣ ለፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ እድገት አስተዋጽኦ በሚያበረክት ሁኔታ መካሄዱን ማረጋገጥ፣ ለብሮድካስት አገልግሎት የተመደበውን ሬዲዮ ሞገድ ማቀድ፣ መመደብ፣ ማስተዳደር፣ ለብሮድካስት አገልግሎት ፈቃድ መስጠት፣ በየጊዜው የሚወጡ ህትመቶች መመዝገብ፣ የብሮድካስት አገልግሎት መሳሪያዎች ስታንዳርድ መወሰን፣ የብሮድካስት ጣቢያ የሚቋቋምበትን ሥፍራ መወሰን፣ ለዘርፉ መስፋፋትና ዕድገት የሚያግዙ ጥናቶች ማካሄድ፣ ዘርፉን የሚመለከቱ መረጃዎችን አጠናቅሮና አደራጅቶ መያዝ፣ በብሮድካስተሮች ላይ የሚነሱ ቅሬታዎችን አጣርቶ ውሳኔ መስጠት ናቸው፡፡
በአዋጅ የተሰጡትን ተግባርና ኃላፊነቶች በሚፈለገው አግባብ ተግባራዊ ለማድረግ የመሠረታዊ የአሰራር ሂደት ለውጥ ጥናት በማከናወን ሙሉ ትግበራ ውስጥ የሚገኝ ተቋም ነው፡፡ በአሁኑ ወቅት የውጤት ተኮር ሥርዓት ትግበራ እና የውጤት ተኮር ምዘናን ሙሉ ትግበራ ለመጀመር በሂደት ላይ ይገኛል፡፡
ባለሥልጣን መ/ቤቱ ከተቋቋመ በኃላ የሬዲዮ ሞገድ እቅድ በማዘጋጀት፣ የፈቃድ አሰራር ስርአት በመዘርጋት 10 የክልል የመንግስት/ የሕዝብ ሬዲዮኖች፣ 4 የመንግስት/የሕዝብ ቴሌቪዥን፣ 5 የንግድ ሬዲዮኖች ፣ 10 ማኅበረሰብ ሬዲዮኖች እና ለ2 የውጭ ፕሮግራሞችን ተቀብለው ለደንበኞች ለሚያደርሱ ፈቃድ ሰጥቷል፡፡ የሕትመት ውጤቶችን በሚመለከት በፌደራል ደረጃ ከሚዘጋጁ ጋዜጦችና መጽሔቶች በተጨማሪ ክልሎች የራሳቸውን ሕትመቶች እያዘጋጁ ያሰራጫሉ፡፡ ከአንድ ክልል በላይ የሚሰራጩ የግል በየጊዜው የሚወጡ ሕትመቶች (ጋዜጣና መጽሔት) በሚመለከት በአሁኑ ወቅት 106 ጋዜጦችና መጽሔቶች በሥራ ላይ ይገኛሉ።
ከዚህም ባሻገር በዘመናዊ የብሮድካስት አገልግሎት መሣሪያ በመታገዝ፣የፕሮግራም ሞኒተሪንግ ሥራ እየሰራ ይገኛል፡፡ለብሮድካስት
አገልግሎት ባለሙያዎች የተለያዩ የአቅም ግንባታ ሥራዎች መሰራታቸው እና በምርጫ ወቅቶች ለተወዳዳሪዎች ነፃ የአየር ጊዜና
የጋዜጣ አምድ ምደባ በተሳካ ሁኔታ ማካሄዱ እንዲሁም የሲቪል ሰርቪስ ሪፎርም በመ/ቤቱ ተግባራዊ እንዲሆን አበረታች ሥራዎች
ተከናውነዋል፡፡ |