|
|
የባለሥልጣኑ የሥነምግባር መከታተያ ክፍል ለአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ሠራተኛና ማሕበራዊ ጉዳይ ቢሮ ስልጠና ሰጠ፡፡
ግንቦት 10/2004 ዓ.ም
|
የባለሥልጣን መ/ቤቱ የሥነምግባር መከታተያ ክፍል ሓላፊ አቶ ግዛው አሰፋ ለአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ሠራተኛና ማሕበራዊ ጉዳይ ቢሮ ሓላፊዎችና ባለሙያዎች የሙስና ምንነት፣ ባህሪያቶችና መገለጫዎች ላይ በቢሮው አዳራሽ በሚያዚያ 09 ቀን 2004 ዓ.ም ስልጠና ሰጥተዋል፡፡
አቶ ግዛው በስልጠናው ሂደት ላይ ስለባለሥልጣን መ/ቤቱ አጠቃላይ መረጃ በማስረዳትና ማንኛውም የህብረተሰብ ክፍል በብሮድካስት አገልግሎት ላይ ያላቸውን ቅሬታም ሆነ ጥቆማ ለባለስልጣን መ/ቤቱ ማቅረብ እንደሚችሉ ገልፀዋል፡፡ |

ስልጠናው በሚሰጥበት ወቅት |
በስልጠናው ላይ የሙስና ባህሪያቶችን ውስብስብ የሚያደርጓቸው ምክንያቶች፣ የሙስና አይነቶችና መገለጫ መንገዶቹ፣ የሙስና መንስኤዎቻቸውና ጉዳቶቻቸው ላይ ሰፊ ማብራሪያ ተሰጥቶ በተሳታፊዎች ውይይት ተደርጎባቸዋል፡፡
ስልጠናው ለቢሮው ሓላፊዎችና ባለሙያዎች በሥነምግባርና በሙስና ላይ ግንዛቤ ለማስጨበጥ ታስቦ የተዘጋጀ መሆኑን የቢሮው የሥነምግባር መኮንን ተናግረዋል፡፡ |
በብሮድካስት ጣቢያዎች በሚተላለፉ ማስታወቂያዎች ላይ የሚታዩ ክፍተቶችን አስመልክቶ ከማስታወቂያ ኃላፊዎችና ባለሙያዎች ጋር የምክክር መድረክ ተዘጋጀ
ግንቦት 1/2004 ዓ.ም
|
ባለሥልጣን መ/ቤቱ በብሮድካስት ጣቢያዎች የሚተላለፉ ማስታወቂያዎች ላይ የሚታዩ ክፍተቶች በተመለከተ ከማስታወቂያ ሓላፊዎችና ባለሙያዎች ጋር የግማሽ ቀን የውይይት መድረክ ሚያዝያ 30 ቀን 2004 ዓ.ም በባለስልጣኑ የመሰብሰቢያ አዳራሽ አካሄደ፡፡
በውይይት መድረኩ በአዲስ አበባ የሚገኙ የብሮድካስት ጣቢያዎችና የኦሮሚያ ሬዲዮና ቴሌቪዥን ድርጅት፣ የማስታወቂያ ሓላፊዎችና ባለሙያዎች ከብሔራዊ ሎተሪ አስተዳደር እና ከኢትዮጵያ የምግብና የመድሃኒት ጤና አስተዳደርና ቁጥጥር ባለሥልጣን ጉዳዩ የሚመለከታቸው ሓላፊዎችና ባለሙያዎች በጠቅላላ 18 ተሳታፊዎች በውይይቱ ተገኝተዋል፡፡
የባለሥልጣን መ/ቤቱ ም/ዋና ዳይሬክተር አቶ ልዑል ገብሩ የመክፈቻ ንግግር ሲያደርጉ “ይህ የውይይት መድረክ በብሮድካስት ሚዲያው የሚሰራጩ ማስታወቂያዎች ምን መምሰል እንዳለባቸው ለመለየት የሚያስችል እና ብሮድካስተሮች በቀጣይ ሕግና አሠራርን ተከትለው በመሥራት ሕብረተሰቡ ከዘርፉ ተጠቃሚ የሚሆንበት ዕድል ለመፍጠር ያስችላቸዋል” ሲሉ መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።
ም/ዋና ዳይሬክተሩ የውይይት መድረክ በብሮድካስት የሚተላለፉ ማስታወቂያዎቹ የሕብረተሰቡን ባሕል፣ ወግ እና እሴቶች ጠብቀውና አክብረው የሚያደርሱበትን መንገድ ለመፍጠር እንዲሁም በሕብረተሰቡ የሚነሱ ቅሬታዎችን ለመፍታት መልካም አጋጣሚ መሆኑን ተናግረዋል።
የመገናኛ ብዙኃን ክትትልና ዓቅም ግንባታ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ሽፈራው ሰሎሞን በማስታወቂያ ዙሪያ የመነሻ ጽሑፍ ያቀረቡ ሲሆን በጽሑፋቸው ውስጥም ማስታወቂያ ሕግና አሠራርን ተከትሎ መሰራጨት እንዳለበት፣ በብሮድካስት ሚዲያዎች የሚተላለፉ ማስታወቂያዎች ፈጥነው ወደ ሕብረተሰቡ የሚድረሱና ተጽእኖ የማድረስ ኃይላቸው ከፍተኛ በመሆኑ ጠንካራ መመሪያና አሠራር እንደሚያስፈልጋቸው እንዲሁም ማንኛውም የሚሰራጭ ማስታወቂያ የሕብረተሰቡን ባሕል፣ ወግ እና እሴቶች ያከበረ ሙያዊ ስነ ምግባሩን የጠበቀ እንዲሆን ሁሉም ተባብሮ መሥራት እንዳለበት አስገንዝበዋል። |

አቶ ሽፈራው ሰሎሞን ለተሳታፊዎች ገለጻ ሲያደርጉ |
አቶ ሽፈራው በገለጻቸው አንድ ማስታወቂያ የሌሎችን ምርትና አገልግሎት የማያንቋሽሽ እንዲሁም ፍትሃዊ የንግድ ውድድር የሚፈጥር መሆን አለበት ሲሉ አክለው ገልጸዋል።
ለውይይቱ በቀረበው ጽሁፍ ላይ ከተሳታፊዎች በርካታ ጥያቄዎችና አሰተያየቶች የቀረበ ሲሆን ለቀረቡት ጥያቄዎች በተሳታፊዎችና በጽሁፍ አቅራቢው በቂ ምላሽ ተሰጥቷቸዋል። ተሳታፊዎቹ እርስ በርሳቸው ከመወቃቀስ ይልቅ ዘረፉን ለማሻሻል በጋራ መስራት እንዳለባቸው ገልጸዋል። በመጨረሻም ተሳታፊዎቹ በሦስት ወር ውስጥ አንድ ጊዜ በመገናኘት በሚታዩ ክፍተቶች ላይ ውይይት በማድረግ ዘርፉን ለማጠናከርና ለማሻሻል እንደሚሰሩ በመስማማት ውይይቱ ተጠናቋል። |
የማህበረሰብ ሬድዮኖች የልማት፣ የዴሞክራሲና የሰላም መድረኮች እንጂ የግለሰቦች እምነትና ሃይማኖት መስበኪያ እንዳይሆኑ ክትትልና ድጋፍ ሊደረግላቸው እንደሚገባ ተጠቆመ።
|
ባለሥልጣን መ/ቤቱ ለቀብሪደሃር እና አካባቢው የሚገኝ ማህበረሰብ የማሕበረሰብ ሬዲዮ ምንነትና አስፈላጊነት እንዲሁም የማህበረሰብ ሬድዮ ጣቢያ ሊከተላቸው ስለሚገባ የህግ ማዕቀፎች ላይ መጋቢት 19 ቀን 2004 ዓ.ም ከ290 በላይ ለሆኑ ተሳታፊዎች ስልጠና ሰጠ።
የማህበረሰብ ሬድዮ ምንነትና አስፈላጊነት በሚል ግንዛቤ ማስጨበጫውን የሰጡት የመገናኛ ብዙሃን ብቃት ማረጋገጫ ባለሙያ አቶ ዘውዱ በዳዳ ሲሆኑ እሳቸውም የማህበረሰብ ሬድዮ የመረጃ፣ የትምህርትና የመዝናኛ ፍላጎቶችን በማሟላት ለዕድገትና ለልማት መፋጠን ጉልህ ሚና እንደሚጫወት ጠቁመዋል።
የማህበረሰብ ሬድዮ ጣብያዎች ሊከተሏቸው የሚገቡ የህግ ማዕቀፎችን በተመለከተ በመገናኛ ብዙሃን ብቃት ማረጋገጫ ቡድን መሪ በአቶ ገብረጊዮርጊስ አብርሃ ማብራሪያ የተሰጠ ሲሆን አቶ ገብረጊዮርጊስ እንዲህ አይነቶቹ ምቹ የህብረተሰብ የውይይት መድረክና የመረጃ ማእከል የሆኑት የማህበረሰብ ሬዲዮ ጣቢያዎች በሃገሪቱ ህጎችና መመሪያዎች ከተመሩ የማህበረሰቡን አመኔታና ተቀባይነት በማግኘት ቀልጣፋና ፍትሃዊ የመረጃ ማዕከል ይሆናሉ ካሉ በኋላ የማህበረሰብ ሬድዮ ጣቢያዎች ለታለመላቸው ዓላማ እንዲውሉ ሕብረተሰቡ ሃላፊነቱን እንዲሸከም ለማድረግ የተጠናከረ የሕዝብ አመራር፣ ክትትልና ድጋፍ እንደሚያስፈልግ ጠቁመዋል።
አያይዘውም የቀብሪደሃር ከተማና አካባቢው ማህበረሰብ አባላት በአካባቢቸው የሚቋቋመው የማሕበረሰብ ሬድዮ ጣቢያ ለልማት፣ ለሰላም፣ ለዴሞክራሲና ለመልካም አስተዳደር መስፈን እንዲሁም ለቋንቋቸው፣ ባህላቸውና እሴቶቻቸው መጎልበት እንጂ ለግለሰቦች መጠቀሚያ እንዳይውሉ ነቅተው ሊጠብቁት እንደሚገባ እና በተግባራዊ እንቅስቃሴው ወቅትም ተገቢውን ክትትልና ድጋፍ እንዲያደርጉለት ጠቁመው የአካባቢው መስተዳድር አካላትም ለሬድዮ ጣቢያው መጠናከር በማህበረሰቡ ከተመረጠው የስራ አመራር ጋር በመተባበር የቅርብ ክትትልና ድጋፍ ያደርጉለት ዘንድ አሳስበዋል።
በስልጠናው ላይ የተገኙት የአካባቢው ማህበረሰብ አባላትም የማህበረሰብ ሬድዮ ጣቢያውን ለማቋቋም በሚደረገው ጥረት ከፌደራል መንግስት ለተደረገላቸው ድጋፍ አመስግነው ሬድዮ ጣቢያው ለጋራ ዕድገታቸው፣ ለሰላም፣ ለዴሞክራሲና መልካም አስተዳደር መስፈን በውይይት መድረክነት እንደሚጠቀሙበትና በሃላፊነት ስሜት እንደሚገለገሉበት ቃል ገብተዋል።
ከስልጠናው በኋላም ሬድዮ ጣቢያውን ለሚቀጥሉት ሶስት ዓመታት የሚመሩ የስራ አመራር ቦርድ አባላት የተመረጡ ሲሆን ለሬድዮ ጣቢያው የሚሆኑ መሳርያዎችም በግዢ ላይ መሆናቸውን ከመገናኛና ኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር ያገኘነው መረጃ ይጠቁማል ።
ይህ የማሕበረሰብ ሬዲዮ ጣቢያ በአገሪቱ የሚገኙ የማሕበረሰብ ሬዲዮ ጣቢያዎችን ቁጥር ወደ 13 ከፍ አድርጎታል፡፡ |
ባለሥልጣን መ/ቤቱ ከባለድርሻ አካላት ጋር የሚያካሂደውን ውይይት አጠናክሮ ቀጥሏል
- ውይይቱ ከባለድርሻ አካላት ጋር ተደጋግፎ ለመሥራት ያስችላል ተባለ!
|
የኢትዮጵያ ብሮድካስት ባለሥልጣን ከባለድርሻ አካላት ጋር የሚያደርጋቸውን የውይይት መድረኮች አጠናክሮ እየሰራ መሆኑን ገለጸ፡፡ ባለድርሻ አካላት ናቸው ተብለው ከተለዩ 5 የአገር ውስጥና ዓለም አቀፍ በጎ አድራጎት ድርጅቶች (NGOs) ጋር በተቋሙ ተግባርና ሓላፊነቶች፣በመገናኛ ብዙኃን አጠቃላይ ሁኔታና በዘርፉ የባለድርሻ አካላት ሚናን በሚመለከት በተቋሙ የመሰብሰቢያ አዳራሽ መጋቢት 27 ቀን 2004 ዓ/ም ውይይት አካሄደ፡፡ |

|
በተካሄደው የውይይት መድረክ የተቋሙ ዋና ዳይሬክተር አቶ ደስታ ተስፋው የባለሥልጣን መ/ቤቱ ተግባርና ኃላፊነቶች፣የተከናወኑ ተግባራትና ያጋጠሙ ችግሮች፣በአገሪቷ የሚገኙ መገናኛ ብዙኃን አጠቃላይ ሁኔታና ባለድርሻ አካላት በዘርፉ ሊኖራቸው ስለሚችሉ አስተዋጽኦዎች በሚመለከት ሰፊ ማብራሪያ ለተሳታፊዎች አቅርበዋል፡፡ ባለሥልጣን መ/ቤቱ ከተቋቋመ በኋላ በመገናኛ ብዙኃን ዘርፍ በርካታ ለውጦች ተገኝቷል ያሉት ዋና ዳይሬክተሩ በአሁኑ ጊዜ 10 የመንግሥት (የሕዝብ)፣5 የንግድና 13 የሚደርሱ የማኅበረሰብ ሬዲዮ ጣቢያዎች ይገኛሉ ብለዋል፡፡ የኢትዮጵያ ቴሌቪዥንን ጨምሮ 4 የቴሌቪዥን ጣቢያዎች በሥራ ላይ የሚገኙ ሲሆን 2 የውጪ ፕሮግራሞችን ተቀብሎ በክፍያ የማድረስ አገልግሎት (Subscription) ለሚሰጡ አካላት ፈቃድ መሰጠቱን ገልጸዋል፡፡ የሬዲዮ ሞገድ ምደባ ዕቅድ ማዘጋጀት፣ የብሮድካስት ጣቢያዎች ስርጭት ሽፋን መወሰን፣የመሣሪያ ተከላ የሚካሄድባቸውን አካባቢዎች መለየት ፣ከአንድ ክልል በላይ ለሚሰራጩ የሕትመት ውጤቶች ምዝገባ ማካሄድ እና በብሮድካስት ጣቢያዎች በሚተላለፉ ፕሮግራሞች ላይ የሚቀርቡ የቅሬታና ጥቆማ አገልግሎት መስጠት የሚሉት ባለሥልጣኑ ያከናወናቸውና ወደፊት አጠናክሮ የሚሄድባቸው ተግባራት እንደሆኑ ዋና ዳይሬክተሩ አብራርተዋል፡፡
ዘርፉን አስመልክቶ በተለያዩ አካላት የተያዘው የግንዛቤ ችግር፣ በዘርፉ በተሰማሩ ባለሙያዎች ላይ የሚታዩ የክህሎትና የአቅም ክፍተቶች እንዳሉ ጠቁመዋል፡፡ በተለይ የሚዛናዊነት ችግር (Imbalancing) ፣ የዘገባ ትክክለኛ ያለመሆን (Inaccurate) እና ወገንተኝነት (partiality) የሚሉት አሁን በሚገኙት መገናኛ ብዙኃን ተቋማት ዘገባዎች ላይ ጎልተው የሚታዩ ችግሮች ናቸው ብለዋል፡፡
እነዚህን ችግሮች ለመቅረፍ የተቋሙን የሰው ኃይልና የማስፈጸም አቅም እንዲሁም በአገራችን መገናኛ ብዙኃን ዘርፍ ለተሰማሩ ባለሙያዎች የአቅም ማጎልበቻ ሥራዎች መሠራት እንደሚኖርባቸው ዋና ዳይሬክተሩ ለተሳታፊዎች ገልጸዋል፡፡ በተለይ የአገራችንን መገናኛ ብዙኃን ከማስፋፋትና ሕግና አሰራርን ተከትሎ የሚሰራን ተቋም ከመገንባት አንጻር በዘርፉ ከተሰማሩ አካላት እንዲሁም ከባለድርሻ አካላትና ከመላው ሕብረተሰብ ጋር ተከታታይ ውይይቶችን ማካሄድ እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል፡፡
አገራችን በተለይ የብሮድካስት አገልግሎቱን ከአናሎግ ወደዲጂታል ለማሸጋገር ሰፊ ሥራ በምታከናውንበት በዚህ ወቅት ከሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ጋር ተቀራርቦ መሥራቱ ተገቢነት ይኖረዋል ብለዋል፡፡ በተጨማሪም ማኅበረሰብ ሬዲዮን ከማስፋፋት አንጻር በርካታ ሥራዎች መከናወን እንዳለባቸው አቅጣጫ ጠቁመዋል፡፡ ይህንንው ለማከናወን ባለሥልጣኑ ባለድርሻ አካላት ብሎ ከለያቸው ተቋማት ጋር ተቀራርቦ ለመሥራት የሚያስችሉትን ጉዳዮች ይዞ እየተወያየና ገንቢ ምላሾችን እያገኘ እንደሆነ ዋና ዳይሬክተሩ ገልጸው ዘርፉን ለማሳደግ ተቋሙ በሚያደርገው እንቅስቃሴ በዕለቱ የተገኙ የበጎ አድራጎት ድርጅት ተወካዮች የበኩላቸውን ድርሻ የሚወጡበትን መንገድ ጠቁመዋል፡፡
ተሳታፊዎች ባለሥልጣን መ/ቤቱ የመገናኛ ብዙኃንን ለማስፋፋት የሚያደርገውን እንቅስቃሴ እንደሚያውቁና ወደፊት ከተቋሙ ጋር መሥራት የሚያስችላቸው በርካታ ጉዳዮች እንዳሉ ገልጸዋል፡፡ በተለይ ብዙዎቹ የብሮድካስት ተቋማት በተለይ ኤፍ ኤም ጣቢያዎች በርካታ ሰዓታቸውን የአውሮፓ ስፖርት እና መዝናኛ ላይ የሚያተኩሩ ሲሆን አገሪቷ በርካታ ሌሎች የልማት፣ የዲሞክራሲና የመልካም አስተዳደር ጉዳዮች እያሉባት በዚህ ጊዜያቸውን ሲያባክኑ እንደሚውሉ ጠቁመው ባለሥልጣኑ ይህንን እየተከታተለ ችግሮቹን ማስወገድ ይኖርበታል ብለዋል፡፡ ለዚህም የሚተበቅባቸውን እንደሚያደርጉ ቃል ገብተዋል፡፡
በዕለቱ በተደረገው ውይይት ከJapan International Cooperation Agency, UNDP-DIP, PACT-Ethiopia, Panos-Ethiopia እና Friedrick Ebert Stiftung ከተባሉ የበጎ አድራጎት ድርጅቶች ተወካዮች በውይይት መድረኩ የተገኙ ሲሆን ከባለሥልጣን መ/ቤቱ ጋር በየጊዜው እየተገናኙ ሥራዎችን እንደሚያከናውኑ ገልጸው የዕለቱ ውይይት ተጠናቋል፡፡ |
ባለሥልጣን መ/ቤቱ ከፌዴራል ሕዝብ ግንኙነት ሓላፊዎች ጋር በመገናኛ ብዙኃን አጠቃላይ ሁኔታ ላይ ውይይት አካሄደ
መጋቢት 21/2004 ዓ.ም
|
መጋቢት 21 ቀን 2004 ዓ/ም ባለሥልጣን መ/ቤቱ ለፌዴራል የሕዝብ ግንኙነት ሓላፊዎች በባለሥልጣኑ ተግባርና ሓላፊነት እንዲሁም በመገናኛ ብዙኃን አጠቃላይ ሁኔታ ላይ የግማሽ ቀን የውይይት መድረክ በተቋሙ የመሰብሰቢያ አዳራሽ አካሄደ።
በውይይት መድረኩ ላይ 70 የሚደርሱ የፌደራል መ/ቤቶች የሕዝብ ግንኙነት ሓላፊዎች እና ተወካዮች የተገኙ ሲሆን የባለሥልጣኑ ዋና ዳይሬክተር አቶ ደስታ ተስፋው የባለሥልጣን መ/ቤቱ ተግባርና ኃላፊነት ፣ተቋሙ ከተቋቋመ ጀምሮ የተገኙ ስኬቶችንና ያጋጠሙ ችግሮችን ፣የአገራችን ሚዲያ የሚገኝበት አጠቃላይ ሁኔታ ፣ የሕዝብ ግንኙነት ሓላፊዎችና ባለሙያዎች ሊገነዘቧቸው የሚገቡ ዋና ዋና ጉዳዮችን ለተሳታፊዎች በዝርዝር አቅርበዋል፡፡ |

|
በአገሪቱ የሚገኙ የመገናኛ ብዙኃን ተቋማት ከሚጠበቀው ብቃት አንጻር የአቅም ውስንነት የሚታይባቸው በመሆኑ ሚዛናዊ መረጃዎችን ለሕብረተሰቡ በማድረስ በኩል የተወሰኑ እጥረቶች እንዳሉባቸው ዋና ዳይሬክተሩ ጨምረው ገልጸዋል። ይህንን ክፍተት ባለሥልጣን መ/ቤቱ ከክትትል ባሻገር የጀመራቸውን የድጋፍ ሥራዎች በማጠናከር ችግሮቹን ለመፍታት ጥረት ማድረግ ያለበት ቢሆንም ሕዝብ ግንኙነቱም ከዚህ በፊት የነበረውን የመረጃ አደረጃጀትና አቅርቦት በማሻሻል ዘመናዊና የተደራጀ የመረጃ ስርአት በመዘርጋት ለሚዲያው ዕድገት የበኩሉን አስተዋጽኦ ማድረግ እንዳለበት አስገንዝበዋል።
ተሳታፊዎቹ በቀረበው የውይይት ሐሳብ ላይ ያሏቸውን ጥያቄዎችና አስተያየቶች አቅርበዋል፡፡ መ/ቤቱ እራሱን በሚፈለገው ደረጃ አለማስተዋወቁ ፣ በመገናኛ ብዙኃን የተሰማሩ ባለሙያዎችን የሚያፈሩ የትምህርት ተቋማት አገሪቷ የምትከተለውን የልማት አቅጣጫ ሊያጠናክር የሚችል የልማታዊ ጋዜጠኝነት ዕውቀት ጨብጠው እንዲወጡ ከማድረግ አንጻር ሊሰሩ እንደሚገባ፣ ከመገናኛ ብዙኃን ባለሙያዎች ጋር በሚፈለገው መልኩ ተቀራርቦ በመሥራትና ያለባቸውን የግንዛቤ ክፍተት ለመፍታት የሚያስችል ስራ ተጠናክሮ መሠራት እንዳለበት ጠቁመዋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም በመድረኩ ቀጣይነት ዙሪያ ከባለሥልጣን መ/ቤቱ ጋር በሦስት ወር አንድ ጊዜ እየተገናኙ ለመወያየት በመስማማት የውይይት መድረኩ ተጠናቋል፡፡ |
« ለውጥ በማምጣት ሴቶችን ማብቃት » በሚል መርህ በተዘጋጀው ታላቁ ሩጫ ላይ የመ/ቤቱ ሴት ባለሙያዎች ተሳተፉ |
የአለም የሴቶች ቀንን ምክንያት በማድረግ ለውጥ በማምጣት ሴቶችን ማብቃት በሚል መሪ ቃል መጋቢት 2 ቀን 2004 ዓ.ም በኢትዮጵያ የታላቁ ሩጫ አስተባባሪነት ለዘጠነኛ ጊዜ በተዘጋጀው የታላቁ ሴቶች ሩጫ ላይ 24 የመ/ቤቱ ሴት ባለሙያዎች ተሳተፉ፡፡
የባለስልጣኑ ሴት ባለሙያዎች የመ/ቤቱን አርማና ስም የታተመበትን ቲሸርት በመልበስ መነሻውንና መድረሻውን አትላስ ሆቴል አድርጎ 5 ኪሎ ሜትር በሸፈነው የታላቁ ሴቶች ሩጫ ላይ በመሳተፍ ተቋሙን የማስተዋወቅ ስራ ሠርተዋል፡፡ |

በሩጫው ላይ የተሳተፉ ሴት ባለሙያዎች በከፊል |
ውድድሩን ታዋቂው አትሌት ሻለቃ ሃይሌ ገብረስላሴና አርቲስት ቻቺ ታደሰ ያስጀመሩት ሲሆን በውድድሩ ላይ ዘጠኝ ሺህ የሚደርሱ ተወዳዳሪዎች ተሳትፈዋል፡፡ የባለስልጣኑ ሴት ባለሙያዎች በውድድሩ በመሳተፍ መ/ቤታቸውን ማስተዋወቅ በመቻላቸው መደሰታቸውን ገልጸዋል፡፡
በሩጫው ላይ ተሳትፈው ከ1ኛ እስከ 3ኛ ደረጃ ለወጡ ተወዳዳሪዎች የገንዘብና የሜዳሊያ ሽልማት የተሰጠ ሲሆን ሌሎች ተሳታፊዎች የሜዳሊያ ሽልማት ተሰጥቷቸዋል፡፡ በሽልማቱ ስነ ስርዓት ወቅት አርቲስት ቻቺ ታደሰ በየዓመቱ የአለም ሴቶች ቀንን ብቻ መጠበቅ ሳይሆን በተገኘው አጋጣሚ ሁሉ ለጤናችን ስፖርት ወሳኝ በመሆኑ ሁሉም በስፖርቱ ተሳታፊ መሆን እንደሚገባው መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡
በመጨረሻም የፎቶ መነሳት ፕሮግራም ተካሂዶ የፕሮግራሙ ፍጻሜ ሆኗል፡፡ |
>ሴቶች በአመራርና በውሳኔ ሰጭነት ደረጃ ለመምጣት ሴቶች ራሳቸውን ማዘጋጀትና ማብቃት እንዳለባቸው ተጠቆመ!፡፡
29 ቀን 2004 ዓ•ም |
ማርች 8 በዓለም አቀፍ ደረጃ ለ101ኛ ጊዜ በአገራችን ለ36ኛ ጊዜ “የሴቶች የተደራጀ ተሳትፎና የላቀ ተጠቃሚነት በዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ትግበራ ይረጋገጣል” በሚል መሪ ቃል የካቲት 29 ቀን 2004 ዓ•ም በባለሥልጣኑ መሰብሰቢያ አዳራሽ ተከበረ።
የባለሥልጣኑ የሥራ ኃላፊዎች፣ ባለሙያዎችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በተገኙበት በዓሉ በተለያዩ ዝግጅቶች ተከብሯል።
የባለሥልጣን መ/ቤቱ ም/ዋና ዳይሬክተር አቶ ልዑል ገብሩ በዓሉን ሲከፍቱ የባለሥልጣኑ ሴት ባለሙያዎች ወደ አመራርነትና ውሳኔ ሰጭነት ደረጃ ለማምጣት ራሳቸውን በሥልጠና ማዘጋጀትና ማብቃት እንደሚጠበቅባቸው ገልጸዋል። ም/ዋና ዳይሬክተሩ የተቋሙ ሴት ባለሙያዎች በአመራርነትና ውሳኔ ሰጭነት ደረጃ ለማምጣት የተለያዩ የድጋፍና የስልጠና ዕቅዶች ተነድፎ በእንቅስቃሴ ላይ እንደሚገኝ ተናግረዋል። |
|
|
የሴቶች፣ የህጻናትና ወጣቶች ጉዳይ ከፍተኛ ባለሙያ ወሮ ሄለን ገ/ዮሃንስ በዓሉን ስናከብር ለሴቶች እኩልነት ሲሉ ህይወታቸውን ያጡትን እያሰብን በሴቶች የተደራጀ ተሳትፎ የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅዱን በማስተግበር የሴቶችን የላቀ ተጠቃሚነት ማረጋገጥ አለብን ሲሉ መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።
የዛሚ 90•7 ኤፍ•ኤም ሬዲዮ ጣቢያ ሥራ አስኪያጅ ወሮ ሚሚ ስብሃቱ በበዓሉ ላይ ተገኝተው ካላቸው የዳበረ ልምድ በመነሳት ሴቶች እኩል የመጠቀምና የመደራጀት መብታቸውን ከማረጋገጥ በዘለለ ወደ አመራርነት እና ውሳኔ ሰጭነት ደረጃ ለመምጣት እንቅስቃሴው ከራሳቸው መጀመር እንዳለበት ተሞክራቸውን አካፍለዋል።
የመ/ቤቱ የስነ ምግባር መኮንን አቶ ግዛው አሰፋ ሴቶችና ሙስና በሚል ርዕስ የግንዛቤ ማስጨበጫ ጽሑፍ ያቀረቡ ሲሆን ባቀረቡት ጽሑፍ ብልሹ አሠራርና ሙስናን ለመዋጋት ከወንዶች በተለየና በተሻለ ሁኔታ የሴቶች ተሳትፎ የጎላ እንደሆነ ተናገረዋል። |
>ለመገናኛ ብዙኃንና ለህዝብ ግንኙነት ባለሙያዎች የግንዛቤ ማስጨበጫ ስልጠና ተሰጠ፡፡
19/06/2004 |
የፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴር ከባለስልጣን መ/ቤቱ ጋር በመተባበር ከየካቲት 15-17 ቀን 2004 ዓ.ም በቢሾፍቱ ከተማ በብሄራዊ እንሰሳት ጤና ጥበቃ እንስቲቲዩት ለመገናኛ ብዙኃንና ለህዝብ ግንኙነት ባለሙያዎች ስልጠና ተሰጠ ፡፡
ስልጠናውን በንግግር የከፈቱት የኢትዮጵያ ብሮድካስት ባለስልጣን ም/ዋና ዳይሬክተር አቶ ልዑል ገብሩ ሲሆኑ በመክፈቻ ንግግራቸውም የመገናኛ ብዙኃንና ህዝብ ግንኙነት ባለሙያዎች በህገመንግስቱ በተለይ በፌዴራል ስርዓቱ ልዩ ባህሪያት፣ ስኬቶችና ተግዳሮቶች ላይ ያተኮሩ መልዕክቶችን ለህብረተሰቡ በማድረስ የፌዴራል ስርዓታችን እንዲጎለብት በማድረግ፣ ግጭትን በመከላከልና በሐይማኖቶችና እምነቶች መካከል መከባበር እንዲኖር በማድረግ ለአገራችን ሁለንተናዊ ዕድገት የሚጠበቅባቸውን ሊወጡ እንደሚገባ ገልፀዋል፡፡
በግንዛቤ ማስጨበጫ ስልጠናው ላይ ህብረብሄራዊ ፌዴራል ስርዓት በኢትዮጵያ፣ ልዩ ድጋፍ የሚሹ ክልሎች የልማት ስትራቴጂ፣ የግጭት መከላከልና አፈታት ፅንሰ ሃሳብ፣ አግባቦችና ነባራዊ ሁኔታ በኢትዮጵያ፣ ሃይማኖት ህገመንግስትና ዴሞክራሲ በኢትዮጵያ፣ የፌዴራል ስርዓቱን ለማጠናከር፤ግጭቶችን ለመከላከል፣ የሃይማኖት መከባበርን ለማስፈን የሚዲያ ሚና፣ የኢትዮጵያ የመገናኛ ብዙኃን ህጋዊ ማዕቀፍ እና ለፌዴራል ስርዓቱ መጠናከርና ለብሔር ብሔረሰቦችና ህዝቦች ሁለናተናዊ አቅም መጎልበት የማህበረሰብ ሬዲዮ ፋይዳ በሚሉት ርዕሶች ላይ ፅሁፍ ቀርቧል፡፡ በቀረቡትም ፅሁፎች ላይ ከተሳታፊዎች ጥያቄዎችና አስተያየቶች የቀረቡ ሲሆን በፅሁፍ አቅራቢዎቹ ምላሽ ተሰጥቶባቸዋል ፡፡ |
|
|
በመጨረሻም የፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴር ሚኒስትር ዶ/ር ሽፈራው ተ/ማሪያም በውይይቱ መዝጊያም ላይ መገናኛ ብዙኃን ህገመንግስቱን አክብረው በመስራት የፌዴራል ስርዓቱን ለማጠናከር ሙያዊ ግዴታቸውን እንዲወጡ አሳስበዋል፡፡ |
የባለስልጣን መ/ቤቱ ባለሙያዎች የ2004 በጀት ዓመት የመጀመሪያ
ስድስት ወራት ዕቅድ አፈጻጸም ላይ ውይይት አካሄዱ፡፡
የካቲት 14/06/04 |
የባለስልጣን መ/ቤቱ ባለሙያዎች በ2004 በጀት ዓመት የእቅድ አፈጻጸም ላይ የመ/ቤቱ የስራ ኃላፊዎች በተገኙበት በመ/ቤቱ የመሰብሰቢያ አዳራሽ ውይይት አካሄዱ፡፡
የባለስልጣን መ/ቤቱ ም/ዋና ዳይሬክተር አቶ ልዑል ገብሩ የ2004 በጀት ዓመት የመጀመሪያው 6 ወር ዕቅድ አፈጻጸምን ያቀረቡ ሲሆን ም/ዋና ዳይሬክተሩ በ6 ወሩ የተከናወኑ ዋና ዋና ተግባራትን ፣ በዕቅድ አፈጻጸሙ የታዩ ጠንካራ ጎኖችና እጥረቶችን እንዲሁም በበጀት ዓመቱ ቀጣይ ስድስት ወራት ትኩረት የሚሹ ጉዳዮችን በዝርዝር አቅርበዋል፡፡ |
|
የእቅድ አፈጻጸም ውይይቱ ሲካሄድ
|
በመቀጠልም በቀረበው ሪፖርት ላይ ከስራ ሐላፊዎችና ባለሙያዎች ጥያቄዎችና አስተያየቶች ተነስተው ለቀረቡት ጥያቄዎች የባለስልጣኑ የስራ ኃላፊዎች በቂ ምላሽ ሰጥተዋል፡፡
ማናጅመንቱና ፈጻሚ ባለሙያው ለአንድ አላማ በመቆም የመ/ቤቱን ተልዕኮ ለማሳካት መስራት እንዳለባቸው ተገልጾ የዚህ ውይይት ዓላማም በማናጅመንቱና በባለሙያው መካካል ያለውን ትስስር በማጠናከር የለውጥ ሠራዊት ገንብቶ በቀጣይ አቅጣጫዎች ላይ የጋራ ግንዛቤ በመያዝ ወደ ስራ ለመግባት እንደሆነ ተብራርቷል፡፡
በመጨረሻም ሁሉም እቅዱን ለማሳካት የሚጠበቅበትን ኃላፊነት እንዲወጣ የስራ ኃላፊዎቹ አሳስበው የውይይቱ መድረክ ተጠናቋል፡፡ |
የባለሥልጣን መ/ቤቱ ባለሙያዎች በአመራርና ስነ ምግባር ላይ የውይይት ፕሮግራም አካሄዱ፡፡
የካቲት 14/06/04 |
የኢትዮጵያ ብሮድካስት ባለሥልጣን ከፌደራል የሥነምግባርና ፀረ-ሙስና ኮሚሽን ጋር በመተባበር የግማሽ ቀን የፓናል ውይይት በባለሥልጣን መሰብሰቢያ አዳራሽ ውይይት አካሄደ፡፡
ፕሮግራሙን አስመልክቶ የመ/ቤቱ የሥነ ምግባር መኮንን የሆኑት አቶ ግዛው አሰፋ የፓናል ውይይቱን ዋነኛ ዓላማ ሲገልጹ በመ/ቤቱ እየተካሄደ ያለውን የለውጥ እንቅስቃሴ ለማፋጠን መልካም ሥነ ነምግባርና የሥራ ዲሲፕሊን የተላበሰ ባለሙያ ለማፍራት የሚያስችልና የግንዛቤ ማስጨበጫ ትምህርቶች በመስጠት የሙስና ትግሉን አጠናክሮ ለማስቀጠል እንደሆነ ገልፀዋል፡፡
የፓናል ውይይቱን በንግግር የከፈቱት የባለሥልጣን መ/ቤቱ ም/ዋና ዳይሬክተር አቶ ልዑል ገብሩ ከተለያዩ ተቋማት የተቋሙን ጥሪ አክብረው ለመጡ የሥነ-ምግባር መኮንኖች ምስጋና ካቀረቡ በኋላ የፀረ ሙስና ትግል የሞት ሽረት ጉዳይ እንደሆነና እንደ መንግሥት፣ እንደ ሀገር ብሎም እንደ ተቋማችን በሥነ ምግባር የታነፀ ባለሙያ መፍጠር ተቋሙ በሚያከናውናቸው ስራዎች ከሐላፊ እስከ ፈፃሚ ባለሙያ ድረስ ሊኖራቸው ስለሚገባ ሥነ ምግባር የፓናል ውይይቱ የሚያደርገው አስተዋፅኦ ከፍተኛ እንደሆነ ጠቁመዋል፡፡ |
|
የፓናል ውይይቱ ሲካሄድ
|
በባለሥልጣን መ/ቤቱ የሚገኙ የሥራ ሐላፊዎችና ባለሙያዎች እንዲሁም የ5 መ/ቤቶች የሥነ ምግባር መኮንኖች በተገኙበት ውይይቱ ተካሂዷል፡፡
የፓናል ውይይቱ በፌደራል የሥነ-ምግባርና ፀረ ሙስና ከፍተኛ አማካሪ የሆኑት አቶ ከበደ ስሜ የቀረበ ሲሆን አመራርና ስነምግባር ምን መምሰል እንዳለበትና መሪዎች በዕድገት ላይ የሚኖራቸው ተፅእኖ ምን እንደሚመስል በስፋት አብራርተዋል፡፡
በመቀጠል በቀረበው ጽሁፍ ላይ የተለያዩ ጥያቄዎችና አስተያየቶች ቀርበዋል፡፡ ለቀረቡት ጥያቄዎች በስነምግባርና የፀረ ሙስና ኮሚሽን ከፍተኛ አማካሪ በቂ ምላሽና ማብራሪያ ተሰጥተዋል፡፡ |
ባለሥልጣን መ/ቤቱ ለሐዋሳና ለሐረማያ ዩኒቨርስቲዎች የማሕበረሰብ ሬዲዮ ፈቃድ ሰጠ!
የሬዲዮ ፈቃድ መሰጠቱ በተቋማቱ ላይ የሚካሔዱ የምርምር፣ የሕብረተሰብ ተኮር እና በአካባቢው የሚካሔዱ የልማት ሥራዎችን ለማፋጠን የጎላ አስተዋጽኦ ይኖረዋል ተባለ። |
ባለስልጣን መ/ቤቱ ጥር 28 ቀን 2004 ዓ∙ም ለሀዋሳ ዩኒቨርስቲ የማሕበረሰብ ተኮር የከፍተኛ የትምህርት ተቋም ሬዲዮ እና ለሀረማያ ዩኒቨርሲቲዎች ከፍተኛ ትምህርት ተቋም ሬዲዮ ፈቃድ ሰጠ።
በምስክር ወረቀት አሰጣጥ ስነ ስርአቱ ላይ የባለሥልጣኑ የሥራ ኃላፊዎችና ባለሙያዎች፣ የዩኒቨርሲቲዎቹ ተወካዮች እንዲሁም ከአሜሪካ ኤምባሲ የተገኙ እንግዶጅ ተካፋይ ሆነዋል።
የባለሥልጣን መ/ቤቱ ዋና ዳይሬክተር አቶ ደስታ ተስፋው የምስክር ወረቀት በሰጡበት ወቅት ባለሥልጣኑ የማሕበረሰብ ሬዲዮ ለማስፋፋት የተለያዩ ተግባራትን ሲያከናውን መቆየቱን አውስተው ዛሬ የተሰጠው ፈቃድ እንዲሁ የተገኘ ሳይሆን ዜጎች በከፈሉት ከፍተኛ መስዋእት እንደሆነ ተናግረዋል። ሬዲዮ ጣቢያዎቹም በአካባቢያቸው የሚገኙ ማሕበረሰቦች በሚከውኗቸው የልማት፣ የዲሞክራሲና የመልካም አስተዳደር ሥራዎች ላይ የጎላ አስተዋጽኦ እንደሚኖራችው ገልጸዋል። የሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚደንት እና የማሕበረሰብ ሬዲዮው የቦርድ ሰብሳቢ ዶ/ር ዮሴፍ ማሞ ዩኒቨርሲቲው በርካታ ሥራዎች እያከናወነ ባለበት ወቅት ፈቃዱ መሰጠቱ ሥራዎቹን በፍጥነትና በጥራት ለመከወን ትልቅ አስተዋጽኦ ይኖረዋል ብለዋል። በተለይ የተቋሙን የምርምር እና የማሕብረሰብ ተኮር ሥራዎች በማገዝ እና አሁን በዩኒቨርሲቲው ለተጀመረው የጆርናሊዝምና የኮምዩኒኬሽን ትምህርት ክፍል ለሚማሩ ተማሪዎች የተግባር ትምህርት ለመስጠት መልካም አጋጣሚ እንደሚፈጥርላቸው አስገንዝበዋል። |
|
|
የሀረማያ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚደንት እና የማሕበረሰብ ሬዲዮው የቦርድ ሰብሳቢ ፕሮፌሰር በላይ ካሳ በበኩላቸው በባለሥልጣኑ እየተከናወነ ያለው የፈቃድ አሰጣጥ ስርአት እጅግ ፈጣንና ቀልጠፋ መሆኑ አመላክተው ሌሎች ፈቃድ አመልካቾችም ይህ ሁኔታ እንደሚገጥማቸው እምነታቸውን ገልጸዋል። እንደ ፕሮፌሰር በላይ ገለጻ ከሆነ የተሰጣቸው ሬዲዮ ፈቃድ በተማሪዎች ያሉ መልካም ተሞክሮዎች ለማስፋት እና በዩኒቨርሲቲው የሚጋጥሙ ተግዳሮቶችን ለመፍታት እንደሚያስችላቸው ተናግረዋል። በተጨማሪም በአካባቢው የሚገኙ ማሕበረሰቦች በሚያከናውኗቸው የግብርና ኤክስቴንሽን ሥራዎች ላይ ድጋፍ ለመስጠት ዋነኛ መሣሪያ ሆኖ እንደሚያገለግል ተናግረዋል። የሬዲዮ ጣቢያው ስርጭት በሦስት ቋንቋዎች ማለትም በአማርኛ፣ በኦሮምኛና በእንግሊዝኛ እንደሚሆን ገልጸዋል።
ባለሥልጣኑ አሁን የሰጣቸውን ሁለቱ የማሕበረሰብ ሬዲዮ ፈቃድ ጨምሮ ያሉት የማሕበረሰብ ሬዲዮ ጣቢያዎች ቁጥር 12 ደርሷል። ከነዚህ ውስጥም ስምንቱ በሥራ ላይ የሚገኙ ሲሆን ቀሪዎቹ ሥራ ለመጀመር በዝግጅት ላይ ይገኛሉ። |